Thursday, April 5, 2018

ለፈገግታና ለታሪክ ትውስታ

ለፈገግታና ለታሪክ ትውስታ



በጌታቸው ታረቀኝ ከተጻፈው አቤቶ ልጅ እያሱ ከሚለው ታሪካዊ ድራማ መግቢያ ላይ የተወሰደ

ገቢር 1
ትዕይንት 1

መብራት ሲጠፋ መጋረጃው ከመከፈቱ በፊት ለተመልካች የሚነበብ

«የተከበራችሁ ተመልካቾቻችን ዛሬ የምትመለከቱት . . . »
መጋረጃ ይነሳል። . . .  በጨለማው ነጋሪት ይሰማል። ጥሩምባ ይሰማል . . . (ጣሴ በባህላዊ የቤተመንግስት ስርአት ለብሶ ይገባል።)

ጣሴ ፦ (በአዋጅ ነጋሪ ስልት) . . .  ስማ ስማ . . . ጆሮ ያለህ ስማ . . .  የሰማህ ላልሰማው አሰማ  . . . ስሚ ስሚ ጆሮ ያለሽ ስሚ . . . የሰማሽ ላልሰማችው አሰሚ  . . . አፈሩ በጎርፍ ተሸርሽሮ እንዳያልቅ አቧራው እየተነሳ በንፋስ እንዳይቦን ከፈረንጅ አገር አስመጥቼ የተከልኩትን የባህር ዛፍ እየዘነጠፍክ ጥርስህን የምትፍቅ የምትፍቂ . . . ጥርስ አባታችሁ ይርገፍና በድዳችሁ ነው የማስቀራችሁ። ቢሻው ጥርሳችሁ በስብሶ ይርገፍ እንጂ የባህር ማዶ ዛፌን እንዳትነኩ ብያለሁ!!! የኮረንቲ መብራት ተከተማው አልፎ በየባላገሩ እንዲደርስ የዘረጋሁትን የመዳብ ሽቦ እየበጠሳችሁ የእጅ አምባርና የጆሮ ጉትቻ የምትሰሩና የምታጌቱ . . . እጅ እና እግራችሁን እያስቆረጥኩ መቀጣጫ ነው የማደርጋችሁ . . . በነገይቱ ተሲአት ደግሞ የንጉሰ ነገስት እያሱ አምስተኛ . . . የንግስ በዓል በታላቁ ቤተ መንግስት ስለሚከበር ሙላሽ ሁላ መጥተሽ ምሳ እንድተበይ ተጠርተሻል!! በማትመጡት ላይ ግን . . .


Tuesday, April 3, 2018

ቆንጆ ሴት ልጅ የወለደው ዔሊ ታሪክ (The Tortoise with a Pretty Daughter - Nigerian folk tale)


ቆንጆ ሴት ልጅ የወለደው ዔሊ ታሪክ
የናይጄሪያ ተረት ተረት
ባንድ ዘመን አንድ እጅግ ኃይለኛ የሆነ ንጉሥ በሁሉም ዘንድ ተፈርቶ ይኖር ነበር። በጣም ኃይለኛ ከመሆኑ የተነሣ የዱር አራዊት እና እንስሳት ሁሉ በጣም ይፈሩት ነበር። በዚያን ዘመን ታዲያ ዔሊ በሁሉም የእንስሳትና የሰው ዘር ዘንድ እንደ ከሁሉም የበለጠ ብልህ እንስሳ እና ከሰዎችም ሁሉ ይበልጥ የተሻለ ጠቢብ ተደርጎ ይገመት ነበር። ይህ በዚያ ዘመን የነበረ ንጉሥም ሃምሳ ልጃገረዶች ሚስቶቹ እንዲሆኑ የዳረለት ኤክፔንዮን የተባለ ወንድ ልጅ ነበረው፤ ሆኖም ግን ልዑሉ ከሚስቶቹ ማናቸውንም አይወዳቸውም ነበር። ንጉሡ በዚህ ነገር በጣም ተበሳጭቶ ማንም ሰው ከልዑሉ ሚስቶች የበለጠች የተሻለች ቆንጆ ልጅ ከወለደ እና አልጋ ወራሹ ከወደዳት ልጃገረዲቱ ራሷ እና አባቷ እንዲሁም እናቷ እንዲገደሉ የሚያዝ ሕግ አወጣ።

ታዲያ ይህን ጊዜ ዔሊው እና ሚስቱ በጣም ቆንጆ የሆነች ሴት ልጅ ነበረቻቸው። ልዑሉ በፍቅሯ ሊያዝ ስለሚችል እናቲቱ እንዲህ የመሰለችውን መልከ መልካም ልጅ አብራቸው እንድትኖር መፍቀዱ ጥሩ አይሆንም ብላ አሰበች። ስለዚህም ልጃቸው መገደልና ጫካ ውስጥ በድብቅ መጣል እንዳለባት ለባሏ ነገረችው። ዔሊው ግን ፍቃደኛ አልነበረም በመሆኑም ዕድሜዋ ሦስት ዓመት እስኪሞላት ድረስ ልጁን ደብቆ አሳደጋት። 

ከእለታት አንድ ቀን ዔሊው እና ሚስቱ የእርሻ ሥራቸውን ለመሥራት ከቤት ርቀው የሄዱ ዕለት፣ የንጉሡ ልጅ በእነርሱ ቤት አካባቢ አደን እያደነ ነበረና በእነሱ ቤት ዙሪያ ላይ ባለው አጥር ጫፍ ላይ ከላይ የተቀመጠ ወፍ ተመለከተ። ወፉ ትንሽየዋን ሕፃን ልጅ እየተመለከተና በውበቷ በጣም ተማርኮ ስለነበረ ልዑሉ ሲመጣ ልብ አላለም። ልዑሉም ወፉን ደጋኑን ወድሮ ቀስቱን በማስወንጨፍ ወፉን መትቶ ሲጥለው ወፉ አጥሩ ውስጥ ወደቀ። በመሆኑም ልዑሉ አንዱን አሽከሩን ወደ ግቢው ውስጥ ገብቶ ወፉን እንዲያመጣለት አዘዘው። አሽከርየው ወፉን ግቢ ውስጥ እየፈለገ ሳለ ድንገት ሕፃኗን ልጅ አያትና በውበቷ በጣም ደነገጠ። ወዲያውኑ ወደ አለቃው ተመልሶ በመሄድ ያየውን ሁሉ ነገረው። ልዑሉ አጥሩን አፍርሶ ገባና ሕፃኗን ልጅ አገኛት፤ እንዳያትም ወዲያውኑ በፍቅሯ ተማረከ። ሚስቱ እንደምትሆን መስማማቷን እስከምትገልጽለት ድረስ ከርሷ ጋር ቆይቶ ለረዥም ጊዜም አዋራት። ከዚህ በኋላ ወደቤቱ ተመልሶ ሄደ ሆኖም ግን ከዔሊው ልጅ ጋር ፍቅር መያዙን በተመለከተ ምሥጢሩን ካባቱ ደበቀው።

ሆኖም ግን በሚቀጥለው ቀን ጠዋት ላይ ዐቃቤ ንዋዩን መልእክት አስላከበትና ስልሳ ቦንዳ ልብስ እንዲሁም ሦስት መቶ ወቄት ወርቅ ወሰደ ከዚያም ይህን ሁሉ ንብረት በገጸ በረከትነት ለዔሊው ላከለት። በመቀጠል ከሰዓት በኋላ ላይ ልክ ምሳ እንደተበላ ወደ ዔሊው ቤት ራሱ ሄደና ሴት ልጁን ሊያገባት እንደሚፈልግ ነገረው። ዔሊው ወዲያውኑ የፈራው ነገር እንደደረሰና ሕይወቱም አደጋ ውስጥ እንደወደቀ ገባው፤ በመሆኑም ንጉሡ ይህን ነገር ካወቀ ራሱን ዔሊውን ብቻ ሳይሆን ሚስቱን እና ሴት ልጁን እንደሚገድላቸው ለልዑሉ ነገረው። ልዑሉ ዔሊው፣ ሚስቱ እና ሴት ልጁ ከመገደላቸው በፊት ራሱ ልዑሉ እንደሚገደል ስለዚህም ይህ እንዲሆን በምንም መልኩ እንደማይፈቅድ መልስ ሰጠው። በስተመጨረሻም፣ ከብዙ ክርክር በኋላ፣ ዔሊው መስማማቱን በመግለጽ ፍቃደኛነቱን አረጋገጠ፤ ብሎም ልጁ ትክክለኛው ዕድሜ ላይ ስትደርስ ሚስቱ እንድትሆን እጇን እንደሚሰጠው ቃል ገባለት። በመቀጠል ልዑሉ ወደ ቤቱ ተመልሶ ሄደና ምን እንዳደረገ ለእናቱ ነገራት። ንጉሡ ልጇ ትእዛዙን እንደጣሰ ያወቀ ጊዜ እንደሚገድለው ስለምታውቅ በጣም የምትወደውን እና የምትኮራበትን አንድ ልጇን እንደምታጣ ስታስበው ከፍተኛ ጭንቀት አደረባት። ሆኖም ግን ንግሥቲቱ ምንም እንኳ ባሏ ምን ያክል ሊናደድና ሊበሳጭ እንደሚችል ብታውቅም ልጇ ፍቅር ከያዘው ልጃገረድ ጋር እንዲጋባላት ፈለገች። ስለዚህም ወደ ዔሊው ዘንድ በመሄድ ልጇ ከሰጠው ጥሎሽ በተጨማሪ በልጇ ፈንታ የተወሰነ ገንዘብ፣ ልብሶች፣ ስኳር ድንች እና የዘንባባ ፍሬ ዘይት ለዔሊው ሰጠችው። ይህን ያደረገችውም ዔሊው ልጁን ለሌላ ወንድ አሳልፎ እንዳይሰጥ ለማድረግ በማሰብ ነበር። 

ለሚቀጥሉት አምስት ዓመታትም ልዑሉ በቀጣይነት ስሟ አዴት ከሚባለው ከዔሊው ልጅ ጋር በቀጣይነት ሲገናኝ ነበር እናም ዕድሜዋ ደርሶ ወደ ጫጉላ ቤት መግቢያዋ ጊዜ ሲደርስ ልዑሉ ለአባቱ፣ ለንጉሡ አዴትን ሚስቱ አድርጎ ሊወስዳት መዘጋጀቱን ነገረው። ይህን ሲሰማ ንጉሡ በጣም ተናደደ። የሚሰጠውን ፍርድም እንዲሰሙ ሁሉም ሰዎች በሆነ የተወሰነ አንድ ቀን ወደ ገበያ ቦታው እንዲሰበሰቡ ትእዛዝ አስተላለፈ። የቀጠሮው ቀን ሲደርስ፣ የገበያ ቦታው በሰዎች ተሞልቶ ነበር እንዲሁም የንጉሡ እና የንግሥቲቱ ድንጋዮች በገበያ ቦታው መሃል ለመሃል ተቀምጠው ነበር።

ንጉሡ እና ንግሥቲቱ ከቦታው ሲደርሱ ሁሉም ሰዎች ከተቀመጡበት ተነሡ እና እጅ ነሡዋቸው። ንጉሡና ንግሥቲቱም በራሳቸው ድንጋዮች ላይ ተቀመጡ። በመቀጠል ንጉሡ አሽከሮቹን አዴት የምትባለውን ልጃገረድ ከፊቱ እንዲያቀርቡዋት አዘዛቸው። ልክ ስትመጣ ንጉሡ በውበቷ በጣም ተደመመ። ልጁ ትእዛዙን ስላላከበረና አዴትን እርሱ ሳያውቅ ሚስቱ ስላደረጋት በጣም መናደዱን ሊነግራቸው እንደሰበሰባቸው ለሕዝቡ ተናገራቸውና ሆኖም ግን አሁን ራሱ መልኳን ስላየውና ቆንጆ መሆኗን ማመን እንዳለበት እና ልጁ ትክክለኛ ምርጫ እንደመረጠ አመነ። በመሆኑም ለልጁ ይቅርታ እንዳደረገለት አስታወቃቸው።

ሰዎቹ ልጃገረዲቱን ሲያዩዋት በጣም ቆንጆ መሆኗን አዩ እና የልዑሉም ሚስት ለመሆን እንደምትመጥን ተረዱ። ለጥቀውም ንጉሡ ያወጣውን ሕግ ሙሉ በሙሉ እንዲሰርዘው ለመኑት። ንጉሡም በሐሳባቸው ተስማማ። ሕጉ የወጣው በ”ኢግቦ” ሕግ መሠረት የወጣ ስለነበር ግን ወደ ስምንት ኢግቦዎች መልእክት ልኮ ካስመጣቸው በኋላ በመላ ግዛቱ ትእዛዙ መሰረዙን ብሎም ማንም ከልዑሉ ሚስቶች የበለጠ ቆንጆ ልጅ ስለወለደ እንደማይገደል ነገራቸው። ሕጉን እንዲሽሩም ለኢግቦዎቹ የዘንባባ ፍሬ ወይን እና ገንዘብ ሰጥቶ አሰናበታቸው። በመቀጠል የዔሊው ልጅ አዴት ልጁን እንደምታገባ አዋጅ አስነግሮ ያንኑ ቀን እንዲጋቡ አስደረገ።

ለሃምሳ ቀናት የቆየ ትልቅ ድግስ ተደግሶ ግብር አበላ፣ ንጉሡ አምስት ላሞችን አሳርዶ ለሕዝቡ እስኪበቃቸው እንዲበሉ እና እንዲጠጡ ብዙ ምግብ እና የዘንባባ ፍሬ ወይን በገንቦ አቀረበላቸው። ሕዝቡም እንደፈለገ በየጎዳናው ላይ ጠግቦ ሰከረ። ሴቶቹ በንጉሡ ቅጽረ ግቢ ዘፈን እና እስክስታ ጨዋታ እየተጫወቱ ሌት ተቀን ለሃምሳ ቀናት ግቢውን አደመቁት። ልዑሉ እና ጓደኞቹም በገበያ ቦታው ላይ ጨፈሩ። ድግሱ ሲጠናቀቅ ለዔሊው ግዛቱ ሆኖ እንዲያስተዳድር ግማሽ ግዛቱን ሰጠው፤ በተጨማሪም ሦስት መቶ ባርያዎችን በእርሻው እንዲሠሩለት በስጦታ መልክ አበረከተለት። ልዑሉ በተጨማሪ ለአማቹ ሁለት መቶ ሴቶችን እና አንድ መቶ ልጃገረዶችን ገረዶቹ ሆነው እንዲያገለግሉት ሰጠው። በዚህም ምክንያት ዔሊው በግዛቲቱ ውስጥ ካሉት ሃብታሞች መካከል አንዱ ሆነ። ልዑሉ እና ሚስቱ ንጉሡ እስኪሞት ድረስ በደስታ አብረው ኖሩና ንጉሡ ሲሞት ልዑሉ በንጉሡ እግር ተተክቶ ነገሠ። እና ይህ ሁሉ ዔሊው ከሁሉም ሰዎች እና እንስሳት ሁሉ ይልቅ ይበልጥ ብልጥ እንደሆነ ያሳያል።

ከታሪኩ የሚገኘው ትምህርት፦ የፈለገውን ያክል ድሀ ብትሆንም ቆንጆ ሴት ልጆችን ከመውለድ አትቦዝን፣ የንጉሡ ልጅ በፍቅራቸው ሊወድቅና የልዑላን ቤተሰብ አባል ሆነው ብዙ ሀብት ሊያፈሩ ይችላሉና።

Friday, March 30, 2018

መሲህ ይመጣል ገና

መሲህ ይመጣል ገና

የያዘ ይዞት ጥላውን ቢሸጠው
ጥላ አይሸጥም'ንጂ ዋለልኝ ማን አለው
የመብራት ልጅ ፋኖስ ማር ነሽ ያሏት
ኃይለመስቀል እንድትሆን ጌጥ ያረጓት
ማር እንደነበር ጌታቸው መች ያኔ ገባቸው
ቼ ብለው ፈረሱን ዘመን ማሰሳቸው
ዓይን ራሱን አለማየቱ መች ያኔ ገባቸው
አይሁድ አላመኑም የጌታን ልጅ አልሰቀሉም
አጭበርባሪውን እንጂ መሲሁን አልነኩም
መሲህ ይመጣል ገና፣ አልቆረጥንም ተስፋ
ሙሴ ይመራናል ሌት ተቀን ሳያንቀላፋ
እያዩ አላዩም ሰምተውም አልሰሙም
ሀብታም ድሀ ቤት በጭራሽ አይገባም


መታሰቢያነቱ ለሁሉም ድሀ ቤት ገብተው ለሞቱ ሀብታሞች

በዕለተ ዑራኤል መጋቢት 2018 (በቊጥር ሲቀለድ)



Tuesday, March 27, 2018

ምርጥ ሐበሻና የዜሮ (የክብ) ትስስርና ከአራት ማዕዘን ቅርጽ ጋ ያለው ነገር


ምርጥ ሐበሻና የዜሮ (የክብ) ትስስርና ከአራት ማዕዘን ቅርጽ ጋ ያለው ነገር

  1. እውነተኛ ሐበሻ ሲወለድም፣ ሲኖርም፣ ሲሞትም ጎጆ ቤት ውስጥ ነው፤ ጎጆ ቤት ቅርጹ ክብ ነው። ኮንዶሚኒየም ያለውን የኑሮና አኗኗር ስኬት እዚህ ላይ ልብ ይሏል። 
  2.  እንደ ተወለደ መሀል አናቱ ላይ ክብ ቅቤ ይደረጋል። በክብ ቅርጽ የተድቦለቦለ ቅቤ ይውጣል። ሁለቱም ዜር ቅርጽ አለው። 
  3.  ዐርባ ወይም ሰማንያ ቀን ሲሞላው ለክርስትናው በክብ ገንዳ ተጠምቆ በክብ እንጀራ ላይ ይንደባለላል።    
  4.  የሚበላው እንጀራ፣ ጢቢኛው፣ ቂጣው፣ ሙልሙሉ፣ አምባሻው፣ ቆጮው፣ ዳቦው የሚጋገረው የግድ በክብ ቅርጽ ነው።     
  5. ወጥ የሚወጣው በክብ ቅርጽ ያለው ጭልፋ ክብ ተሠርቶ ነው። ገንፎም የሚቀርበው በክብ ቅርጽ መሃሉ ላይ ክብ ጉድጓድ ተበጅቶ ቅቤ ፈሶበት ነው።    
  6.  ሐበሻ ሲያድግ ቁንጮ ተላጭቶ ነው። ቁንጮ ክብ ቅርጽ ነው። አሁንም ከዜሮ አልራቀም።    
  7.  ሐበሻ አንገቱ ላይ ክርስቲያን ከሆነ ማእተብ፣ ሲልም ጥምጣም ወይም ሙስሊም ከሆነ ቆብ አያጣውም።    
  8.  ቄስ ትምህርት ሲማር ዛፍ ሥር ክብ ሠርቶ ነው። ክብ ሆኖ የተማረው ዕድሜ ልክ እስከ ዕለተ ሞቱ የማይስተው በደንብ የሚገባው ትምህርት ነው። አራት ማዕዘን ክፍል ሆነ በአራት ማዕዘን ሠሌዳ ተምሮ ለውጥ ሲያመጣ አላየንም። ለምለሚቱ አገሬ እያለ ትላንትም ሲረዳ ነበር ዛሬም ይረዳል።   
  9.  አይሮፕላን ክብ ቅርጽ ስላለው የኢትዮጵያ አየር መንገድ በዓለም ውስጥ ካሉ ምርጥ አየር መንገዶች አንዱ ለመባል ቢችልም ያንኑ አይሮፕላን ያበረረ ድንቅ ሐበሻ አብራሪ መኪና ሲይዝ ሥርዓት ሲጥስ ወይም አደጋ ሲደርስበት ብሎም አደጋ ሲያደርስ ይታያል፤ ምክንያቱም መኪና ቅርጹ አራት ማዕዘን ነው። ሐበሻ የአራት ማዕዘን ነገር አለርጂክ ነው ብለናል።   
  10.  ቤተክርስቲያኑ መስጊዱ ሁሉ ክብ ቅርፅ ነው። አራት ማዕዘን ከሆነ መጤ ስለሆነ ችግር ፈጣሪ ነው።     
  11.  እንስራው፣ ድስቱ፣ ምንቸቱ፣ አገልግሉ፣ ጣሳው፣ ስኒው፣ ሽክናው፣ ማክዳው፣ የቤት ቁሳቁሱ ሁሉ ክብ ነው።    
  12.  አፈርሳታ፣ ዳኝነቱ፣ ጉባኤው የሚከናወነው ክብ ሠርቶ ተቀምጦ ፊት ለፊት እየተያየ ነው። በአራት ማዕዘን አቀማመጥ ውጤታማ መሆን አይቻልም።    
  13.  ክብ የማይሠሩ ነገሮች እንኳ ቢኖሩ የግድ በተራ መዞር አለባቸው። ለምሳሌ፦ ጽዋ፣ ጉዳይ ለማስፈጸም ቢሮ መሄድ፣ ማኅበር፣ ዕቁብ፣ ዕድር ወዘተ።  
  14.  ሐበሻ በአራት ማዕዘን ቅርጽ አንድ ነገር ከሠራ እጅግ የመረረ ቁምነገር ወይም አስፈሪ ጉዳይ ነው። ለምሳሌ፦ ክታብ፣ ሬሳ ሣጥን፣ መቃብርና የመቃብር ድንጋይ፣ ብራና መጽሐፍ፣ መስቀል ወዘተ።    
  15.  በአራት ማዕዘን ቅርጽ የሚዘጋጁት ነጠላ፣ ኩታ፣ ጋቢ፣ ጃኖ የክት ናቸው። ዝም ተብሎ አይለብሱም።   
  16.  የጥንት ባሕላዊ ሥዕሎች በሙሉ እንደሚያሳዩት ሰው ፊቱ ቅርጽ ክብ ነው። ሁሉ ነገሩ ክብ ነው። ወይም ለክብ የተጠጋ ነው።   
  17.  ክብ (ቀለበት) ያለበት ፊደል ሳይጠቀሙ ምንም የተሟላ ዓርፍተ ነገር በግዕዝ፣ በትግርኛ ሆነ በአማርኛ ወዘተ መጻፍ አይቻልም።   
  18.  አክሱም ሐውልት ጫፉ ክብ ነው። ላሊበላ የተፈለፈለው ክብ ቅርጽ ባለው መሬት ውስጥ ተከቦ ነው።   
  19.  የንጉሥ እና የንግሥት ዘውድ ክብ ነው። አራት ማዕዘኑን ያደርጉ ወይም ምንም ያላደረጉ ታሪካቸው በስተመጨረሻ አጉል ነው። ምሳሌ፦ አፄ ዩሐንስ።  
  20.  ጦር ይዞ የግድ ጋሻ መጨመር አለበት። ክብ ከሌለ ትጥቁ አይሟላምና። ለሴቷ መቀነት፣ ለወንዱ ዝናርን መጨመር ይቻላል።   
  21.  ሐበሻ ሲበላ፣ ሲጠጣ፣ ሲያማ፣ ሲያጠቃ፣ ሲወር ወዘተ የግድ ክብ ሠርቶ ነው።   
  22.  ሰውን ሲቀብር የግድ ክብ ሠርቶ በመቆም ነው።  
  23.  ኢትዮጵያ የሚለው ቃል ራሱ ሦስት ክብ ነገር፣ ጎጃም ሦስት፣ ኦሮሞ ሦስት፣ ወላይታ ሦስት፣ ትግራይ ሁለት፣ አማራ ሁለት፣ ሸዋ ሁለት፣ ጐንደር ሁለት፣ አደሬ ሁለት፣ ጉራጌ አንድ፣ አፋር አንድ ክብ ነገር አላቸው።   
  24. ቀን መቊጠሪያው ልክ እንደ ሰዓት በእኩል ሠላሳ ቀናት ተከፋፍሎ ክብ ሠርቶ ሲገጥም አንድ ዓመት ይሆናል።   
  25.  በስፖርት ሜዳ መዞርን (አምስት ሺህ ወይም ዐሥር ሺህ) ወይም ከተማ መዞርን (ማራቶን) የተመለከቱ ስፖርቶች ከሆኑ ማንም አይችለውም። ምሳሌ፦ እንደ እግር ኳስ ያሉ ግን በአራት ማዕዘን ሜዳ፣ በአራት ማዕዘን ግብ የሚጫወቱ ጨዋታዎች መቼም አይቀናውም። በተመሳሳይ መልኩ ገበጣንና ቼዝን ልብ ይሏል።