Saturday, March 30, 2019

Facebook በእኔ ዕይታ


(ያልተከሸነ ረቂቅ ጽሑፍ)
ለአብዛኛው አንኮ የኛ ትውልድ Facebook ላይ ያለው ቁምነገር በአጭሩ እንዲህ ነው፦

"እይ፥ ተመልከት ሕይወቴ ካንተ የተሻለ ነው። ምንም ልጻፍ ምን ፣ ሳትወድ በግድህ አንብብ ! እኔ ካንተ የተሻለ አውቃለሁ። ይኼን እውነት ማለትም እኔ ካንተ የተሻለ እንደማውቅ አንተም አሳምረህ ታውቃለህ። አይደለም ብለህ ግን አንዲት ቃል ትንፍሽ ብትል እስከ ዘር ማንዘርህ አጥረግርጌ እሞልጭኸለሁ።" በሚል ጠብ ያለሽ በዳቦ ጭብጥ የተሞላ ዘመናዊ ታዳሚውን አሳታፊ ጉራና ሽፍጥ የተሞላ መደዴ ተውኔት ነው።

እንደሚታወቀው የፌዝቡክ (ግድፈቱ ለነገር ነው) ፈልሳፊውና ባለቤት ከነጓደኞቹ ሐሳቡ የመጣላቸው በመጸዳጃ ቤት ግድግዳ ላይ ከሚለቀለቁ ጽሑፎች እንደሆነ ዓለም ያወቀው ፀሐይ የሞቀው የአደባባይ ምሥጢር ነው። ይህ አባባል በቻይንኛ ፈስ-ቡክ (አሁንም ግድፈቱ ሆን ተብሎ ነው) ፖፖና ውኃ ፍሳሽ የሌለው በሳይበር ቴክኖሎጂ በየጉራንጉሩ የሚገባ የመፀዳጃ ቤት ፍሳሽም ነው ማለት ነው። ምን ለማለት ተፈልጎ ነው ፥ ብዙ ሰዎች በአደባባይ ማለት ወይም መናገር የማይፈልጉትን ወይም ማድረግ የማይችሉትን እንዲናገሩና እንዲያደርጉ ዕድል ተሰጥቶዋቸዋላ!

ፌዝቡክ ሆነ ፈስቡክ እንዲህ እንደ ዛሬው መለስተኛ ምናባዊ የጦር አውድማ ከመሆኑ በፊት፣ እንዲህ እንደ ዛሬው ራሱን የቻለ ስድስተኛ መንግሥት ከመሆኑ በፊት አጀማመሩ ላይ እንደ ዓላማ አድርጎ የተነሣው የተጠፋፉ ጓደኛሞችን ማገናኘት፣ ከዘመድ አዝማድ እንዲሁም ከባለንጀሮችና ዕውቂያዎች ጋር ወቅታዊ የግል መረጃን በመለዋወጥ እንደተቀራራቡ መቆየት የሚያስችል ቅንነት  ያለው የሚመስል አዲስ የቴክኖሎጂ እመርታ ነበር። (ድርጅቱ የሰዎችን ገመና እየሸጠ ድንቡሎ ግብር ሳይከፍል ቢሊዮኔር መሆን መቻሉ ምሥጢር ለጊዜው ይቆይልን።)

መተግበሪያው ሳይውል ሳያድር ግን እንደ ፔን ፍሬንድ የመሳሰሉ ጥንታዊ ከአዲስ ሰው ጋር መተዋወቂያ መድረኮችን ሁሉ በመተካት፣ በቅፅበት ውስጥ በሺዎች የሚቆጠሩ ጓደኛ ተብዬ የፌዝቡክ ጀሌዎችን ማፍራት ከማስቻሉ ባሻገር እንደ ሜም፣ ጥቅሳጥቅስ የመሳሰሉ ፈጣን መዝናኛና መማማሪያዎችን በማካተት እንደ ሪያሊቲ ሾው ሁሉ ሰው ሲዘለፍ ሲሸወድ ወዘተ ማሳየት ከመቻሉ ጋር ተይይዞ ከመዝናኛነትም አልፎ ወደ ሱስነት ደረጃ ከፍ በሚል ሁኔታ የዘመኑ የሰው ልጅ አንዱና ዋንኛ መገለጫ መሆን የሚችልበት ደረጃ በፍጥነት በመሸጋገር ላይ ነው።

እኔ ፌስቡክ አልጠቀምም የሚሉ ሰዎች በተለያየ መንገድ አልጠቀምም ቢሉም አጮልቀው የሚያዩ መሆናቸው እንደተጠበቀ ሆኖ ከናካቴው ምንም የሌሉበትም ቢሆኑ እንኳ ባንድ ወይም በሌላ መልኩ የፈስቡክ ተፅእኖ ሰለባ ናቸው። ሐሰተኛ የፌስቡክ ተጠቃሚዎችን ጨምሮ ጠቅላላው የፌስቡክ ተጠቃሚ በዓለም ከሁለት ቢሊዮን በላይ እንደሚሆኑ ልብ ካሉ ዘንዳ ከዓለም ሕዝብ ብዛት ነፍስ ያወቀው አንድ አራተኛው መጠቀሙን እግረ መንገድዎን ያስታውሱ።

የፈስቡክ ልክፍትና ሱሰኝነት እንዴት እንደሚጀምርና ካንዱ ወደ አንዱ እንዴት እንደሚጋባ የሥነ ልቦና ባለሙያዎች ገና እያጠኑት ያለ ሰፊ ምርምርና ጥናት የሚጠይቅ ዓለማችን በዚህ ዘመን የገጠማት የጋራ ማኅበራዊ ቀውስ ዋንኛ ምንጭ ነው።

የፀደይ አብዮት በመባል የሚታወቀው ሰደድ እሳት ቱኒዚያ ውስጥ በመሃመድ ቦአዚዚ ራስን ማቃጠል ሲነሣ ከአብዮቱ ጥንስስ ጀምሮ እስከ እንደ ሊቢያና ሶሪያን ሲያፈራርስ ፈስቡክ የአብዮቱ ዋንኛ ጦር መሣሪያ ነበር። በአሜሪካና የአውሮፓ ሃገራት የፕሬዝዳንታዊ ምርጫ ላይ የነበረው ሚናም በዋዛ አይታይም። እዚህ ባገራችንም እነ ቄሮ፣ ፋኖ፣ ዘርማ ምን እንደሠሩበት የቅርብ ጊዜ ትዝታችን ነው።

ፌስቡክ ለሰው ልጅ ይዞት የመጣው ገጸበረከት፦ ጊዜና ገንዘብ ቆጣቢ፣ ለአጠቃቀም ምቹ መሆኑ፣ ፍጥነት ያለው የመልእክት ትልልፍ ዘዴ መሆን መቻሉ አንዱና ዋንኛው ነው። በተረፈ የዘመኑ ሰው ትግሥት የምትባለውን እንደ መቅበሩ በተለያየ ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ማኅበራዊ ምክንያት ቅንዝንዝ፣ ባለበት የማይረጋ፣ ችኩል ከመሆኑ ጋር የዚህ መተግበሪያ መፈጠር ሰኔና ሰኞ ሲገጣጠሙ ዓይነት ነገር ሆኗል።

በአጭሩ ሐተታ አይወድም ትውልዱና ጊዜው። ቁንፅል ነገር በልቶ ቁንፅል ነገር ይዞ ሩጫ (ፋስትፉድና ቪትስን እዚህ ላይ ልብ ይላሉ)። ምግባችን ፋስት ፉድ፣ ትምህርታችን ገለብ፣ ገለብ፣ ሥራችን ዝምብሎ ሩጫ ብቻ።

ፈስቡክ ጥሩ የሐሜት ሱስ መወጣጫም ነው። አንዱን ታዋቂ ወይም አንዷን ባለዝና ወርተራ ጠብቆ አፈር ድቤ ማብላት ቀላል ነው። ከዚህ በተረፈ የተለያየ ድብቅ ጥምን እና ነውርን ባደባባይ ማራመጃ መንገድም ነው ፌስቡክ። (ያው እንደሚታወቀው በሕፃናት ወሲብ ልክፍት የተለከፈ ወንጀለኛ፣ ከእንስሳት ጋር አጓጉል ድርጊት የሚፈጽም፣ የሰው ደም በማፍሰስ የሚረካ፣ ወዘተ እያለን ዘርዝረን አንጨርሰውም። የሰው ልጅ ድብቅ ሱስ ብዙ ነው ብለን እንለፈው)።

ዕብደት ማለት አንድ ተመሣሣይ ነገር እያደረጉ የተለየ ውጤት መጠበቅ መሆኑን ምሁራን ደጋግመው ተናግረውታል፤ እኛም ደጋግመን ሰምተነዋል። ምን ያክሎቻችን ምንም በዕለት ተዕለት ሕይወታችን ፋይዳ እንደሌለው እያወቅን እንጠቀምበታለን?

ዕብደት ብቻ አይደለም ያልሆንከውን መሆን ራሱ የዕብደት ጥግ መድረስ ምልክት ነው። ስንቱን ሐሳዊ ጋዜጠኛ፣ ሐሳዊ ሰብአዊ መብት ተሟጋች፣ ሐሳዊ ብሔርተኛ፣ ሐሳዊ አፍቃሪ፣ ሐሳዊ የአካባቢ አየር ተቆርቋሪ፣ ሐሳዊ ፓሊስ መርማሪ፣ ሐሳዊ ፖለቲከኛ፣ ሐሳዊ ታሪክ ጸሐፊ፣ ሐሳዊ ዐቃቤ ቅርስ፣ ሐሳዊ ታቦት አንጋሽ፣ ሐሳዊ ፓስተር ሰባኪ፣ ሐሳዊ አገር አቅኚ ሐሳዊ ወዘተ ሲሆን አይተናል። ምን ያላየነው አለ? እዚህ ዕብዶችና ወሬኞች፣ ሥራ ፈቶችና አስመሳዮች ባጥለቀለቁት የተበላሸ ምናብ መንደር ምን የሌለ አለ?

ቁርስ፣ ምሳና እራታችንን የምንበላበት ምግብ ቤት፣ አዲስ ልብስና ጫማ የምናስመርቅበት ቡቲክ፣ ቪዛ የምናስመታበት ኬላ፣ በግና ዶሮ ተራ፣ ላልታመምነውን እንዳንታመም መክረው የሚያሟርቱብን፣ ቀን መቁጠሪያ (ዛሬ እንትን ነው ነገ እንትና እንኳን አደረሳችሁ መባበያ)፣ ሚስትን ወይም ባልን እቅፍ አድርገው ፎቶ ተነሥተው መገለጫ (ፕሮፋይል) አድርገው ከመሬት ተነሥተው ትነካውና ትነካትና የሚመስል ዓይነት ዛቻ የምናሰማበትና የምናይበት፣ የልጆች ዕድገት የምንዘግብበት፣ ትኩስ የወሬ ምንጭ፣ ነጻ ጋዜጣ፣ ለቅሶ ቤት፣ ሰርግ ቤት፣ መቀጣጠሪያ፣ መጀናጀኚያ፣ ፍርድ ሸንጎ፣ ሕፃናት ማዋለጃ ክፍል፣ ሆስፒታል፣ የጽድቅና ኩነኔ መመዝገቢያ ባሕረመዝገብ ይመስል የተሳለሙትን ደብር፣ ያደረጉትን በጎ ምግባር የምንከትብበት፣ እቃ የምናሻሽጥበት፣ መፈንቅለ መንግሥት፣ የባለሥልጣን ሹም ሽር የምናደርግበት . . . ምን የማይባል፣ ምን የማይደረግ ነገር አለ እዚህ መንደር? ዓለምን እንደ መርካቶ ብናስባት ምናለሽ ተራ ነው በአጭሩ ፌስቡክ።

ፌስቡክ ዕልም ያለ የቀለጠው መንደር ሆኗል። እዚህ መንደር ያገር ሽማግሌ፣ የሃይማኖት አባት፣ ታላቅ ታናሽ፣ መሪ ተመሪ፣ ዳኛ፣ ፖሊስ የሚባል ነገር የለም። በራሱ ሕግ፣ በራሱ ቴምፖ፣ በራሱ ዜማ ስልት፣ በራሱ ሥርዓት ይመራል።

ለማንኛውም ወዳጄ ልቤ ከዚህ እንደ ስሙ ፌዝቡክ ነውና ብዙ አትጠብቅ። ፈስቡክ ዳቦ አይሆንም። ለወሬ የለው ፍሬ ለአበባ . . . ይባል የለ ከነተረቱ። ዋዛና ፈዛዛም ሲበዙ ቤት ሊያፈርሱ ይችላሉና ቆጠብ ማለቱ ለሁሉም ሳይበጅ አይቀርም። ዳይ ወደ ሥራ። ሥራ ባይኖር እንኳ አንበብ ነገ የምትመነዝረውን ሀብት ይሰጥሃል።
ከሣቴ ብርሃን ቡሩህ በዕለተ ማርያም የመጋቢቷ (2019)

Thursday, March 28, 2019

ከበሮና የሰው ልጅ ተመሳሌታዊ ዝምድና


ከበሮ በሥዕሉ ላይ እንደሚታየው ሦስት ዋንኛ ክፍሎች አሉት። አፉ ሰፋ የሚለው እና በዋንኛነት የሚመታው "ደባይ" ሲባል ሁለተኛው ጫፍ ጠበብ የሚለው እና ከጸናጽል ጋር እየተንሰላሰለ አልፎ አልፎ ምትን ለመጠበቅ ብቻ የሚነካው ወይም የሚመታው "ጥራይ" ይባላል። የከበሮውን አብዛኛውን ክፍል የሚሸፍነው ሆዱ ደግሞ "ከርሰ ከበሮ" ወይም "የድምፅ ሳጥን" በመባል ይታወቃል። 

የሰው ልጅም በአጠቃላይ ሲታይ በእነዚህ ሦስት የከበሮ ክፍሎች ተለይቶ ሊታይ ይችላል። ሕይወት ደግሞ እንደ ከበሮ መቺው። ደባይ የሚባለው ክፍል ታዋቂ ሰዎችን፣ ዝነኖችን፣ ፖለቲከኞችን፣ የሃይማኖት መሪዎችን፣ ባለልዩ ተሰጥዖ ሰዎችን ወዘተ ይወክላል። ምንም ያድርጉ ምን ጩኸታቸው ገኖ ቁልቁል እስከ ታች ይሰማል።ሦስተኛው ክፍል "ጥራይ" ደግሞ የለየለትን መናጢ ድሃ ይወክላል። ችግሩ ጥርስ ሲያወጣ፣ ጠኔው ሲበዛ ወደ ላይ ዘልቆ የላይኛውን ክፍል ደባዩን ቀልብ ይስባል። 

መሀለኛው ክፍል ማለትም ከርሰ ከበሮው ደግሞ በተለምዶ "አማካይ" የሚባለውን ወይም "መካከለኛውን ክፍል" ይወክላል። ከላይና ከታች የሚመጣውን ድምፅ ያስተጋባል። በሁለቱ ጠርዞች መካከል ያለውን ግንኙነት ወዲህና ወዲህ እያለ ድምፃቸውን በማቀባበል አንድ ወጥ ዜማ እንዲሰማ የበኩሉን ድርሻ ይወጣል።
ሕይወት በፈለገችው ምት እየደበደበች በነፍስ ወከፍና በጅምላ ከእያንዳንዱ የሰው ልጅ መስማት የምትፈልገውን ዜማ ትሰማለች። እያንዳንዱ ዘመንም የየራሱ ከበሮ ይኖረዋል። ለምሳሌ የግሪክ የዴሞክራሲ ዘመን፣ የሮማ ዘመን፣ የመስቀል ጦርነት፣ የተሃድሶ ዘመን፣ አንደኛ የዓለም ጦርነት፣ ሁለተኛ የዓለም ጦርነት፣ ቀዝቃዛው ጦርነት፣ ሽብርተኝነት፣ ግሎባይላይዜሽን እያለ ይቀጥላል።

ደባዮች ገነው ይጮኸሉ። ጥራዮችም በአቅማቸው የደባይን ምት ይቆጣጠራሉ። መሃል ሰፋሪዎችም መሃል ላይ ሆነው ሁለቱን ጫፍ ሲያዳምቁና ሲያደንቁ ይኖራሉ። ሁሉም ሕይወት የቀመረችላቸውን ዜማ እየተደለቁ አዚመው ያልፋሉ።

ከሣቴ ብርሃን ቡሩክ በዕለተ ገብሪኤል (2019 በራስ አቆጣጠር)
መነሻ ሐሳብ THE SUBTLE ART OF NOT GIVING A F*CK
Image may contain: food

Thursday, March 21, 2019

World Happiness Report 2019 የዓለም የደስተኛነት ሪፖርት 2019 እአአ

World Happiness Report 2019
የዓለም የደስተኛነት ሪፖርት 2019 እአአ
በደስተኛነት ደረጃ ከ156 አገሮች 134ኛ ብንሆንም የሚገርመው ግን ግብፅ፣ ኡጋንዳ፣ ህንድ፣ ማዳጋስካር፣ ሩዋንዳን ከመሳሰሉ አገሮች መሻላችን ደግሞ "እፎይ፣ ተመስገን !" የሚሉት ባህላችን ይሆን ያተረፈን? አሁንም ተመስገን በሉ ! ከኛም የከፋ አለና።
ከኛ በታች ያሉ አገሮች በጣም አንደኛ ከከፋት ከደቡብ ሱዳን ጀምሮ እስከ 134ኛ እኛ ድረስ ዝርዝሩ ከታች ወደላይ ይህን ይመስላል፦
156. South Sudan(2.853)
155. Central African Republic(3.083)
154. Afghanistan(3.203)
153. Tanzania(3.231)
152. Rwanda(3.334)
151. Yemen(3.380)
150. Malawi(3.410)
149. Syria(3.462)
148. Botswana(3.488)
147. Haiti(3.597)
146. Zimbabwe(3.663)
145. Burundi(3.775)
144. Lesotho(3.802)
143. Madagascar(3.933)
142. Comoros(3.973)
141. Liberia(3.975)
140. India(4.015)
139. Togo(4.085)
138. Zambia(4.107)
137. Egypt(4.166)
136. Uganda(4.189)
135. Swaziland(4.212)
በጣም ደስተኛዎቹ ደግሞ አነሆ፦
50. Romania(6.070)
49. Ecuador(6.028)
48. Cyprus(6.046)
47. Romania(6.070)
46. Argentina(6.086)
45. Kosovo(6.100)
44. Nicaragua(6.105)
43. Slovenia(6.118)
42. Colombia(6.125)
41. Lithuania(6.149)
40. Uzbekistan(6.174)
39. Poland(6.182)
38. Trinidad and Tobago(6.192)
37. Slovakia(6.198)
36. Bahrain(6.199)
35. Italy(6.223)
34. El Salvador(6.253)
33. Singapore(6.262)
32. Uruguay(6.293)
31. Brazil(6.300)
30. Panama(6.321)
29. Spain(6.354)
28. Qatar(6.374)
27. Saudi Arabia(6.375)
26. Guatemala(6.436)
25. Chile(6.444)
24. Taiwan Province of China(6.446)
23. France(6.592)
22. Mexico(6.595)
21. Malta(6.726)
20. United Arab Emirates(6.825)
19. Czech Republic(6.852)
18. United States(6.892)
17. Belgium(6.923)
16. Germany(6.985)
15. Ireland(7.021)
14. United Kingdom(7.054)
13. Luxembourg(7.090)
12. Israel(7.139)
11. Costa Rica(7.167)
10. Australia(7.228)
9. Austria(7.246)
8. Canada(7.278)
7. New Zealand(7.307)
6. Sweden(7.343)
5. Switzerland(7.480)
4. Netherlands(7.488)
3. Iceland(7.494)
2. Norway(7.554)
1. Denmark(7.600)
ሙሉ ዝርዝሩን ከዚህ በታች ማግኘት ይቻላል
https://s3.amazonaws.com/happine…/…/WHR19_Ch2A_Appendix1.pdf

Saturday, March 16, 2019

Brook Beyene: Arthur Rimbaud’s poems and works have been transla...

Brook Beyene: Arthur Rimbaud’s poems and works have been transla...: The French President Emmanuel Macron and the Ethiopian Prime Minister Dr. Abiy Ahmed leafing through the library edition of Passages. Passa...

Arthur Rimbaud’s poems and works have been translated by Brook Beyene

The French President Emmanuel Macron and the Ethiopian Prime Minister Dr. Abiy Ahmed leafing through the library edition of Passages. Passages (Bernard Dumerchez publishing house) is the French presidential gift to the Ethiopian Prime Minister. This is the first translation into Amharic of the French poet Arthur Rimbaud, who lived 10 years in Ethiopia and the Horn of Africa (1881-1891). Arthur Rimbaud’s poems and works have been translated by Brook Beyene, François Morand and Dr. Berhanu Abebe, and edited and prefaced by Alain Sancerni and Jean-Michel Le Dain. A co-edition has been published in Ethiopia with Shama Books and the French Embassy support.
On the same occasion, the library edition of Rimbaud selon Harar by Alain Sancerni and the artist Joël Leick (Bernard Dumerchez publishing house), has been given by the French President to the Ethiopian President Mrs Sahle Work Zewde.
N.O.E., 13/03/2019
Photo : le Monde, 12/03/2019

Image may contain: 4 people, including Zelalem Getahun, people smiling, suit

Tuesday, March 12, 2019

የሞት ውበቱ ፲፬ - የካሃሊል ጂብራን ግጥም


የሞት ውበቱ ፲፬ - የካሃሊል ጂብራን ግጥም
(መታሰቢያነቱ በበራራ ቊጥር ET 302 መጋቢት 1 ፥ 2011 ከዚህ ዓለም በሞት ለተለዩት 157 መንገደኞች) 
ትርጉም፦ በብሩክ በየነ

ክፍል አንድ - ጥሪው
በፍቅር ሰክራለችና እፎይ ትበል ነፍስያዬ ትተኛበት
ትረፍበት መንፈሴ ስለነበራት የቀንና ሌሊት ቸርነት ፤
ባልጋዬ ዙሪያ ሻማዎቹን ለኩሱዋቸው፣ እጣኑንም አጫጭሱ
የጠምበልልና የጽጌሬዳ አበባ ቅጠል በላዬ ላይ ነስንሱ፤
ጸጒሬንም በሉባንጃ ሞጅራችሁ ቅበሩት፤ እግሬንም ሽቶ ቀቡት
መላከ ሞት በእጁ ግንባሬ ላይ የጻፈውን ጮክ ብላችሁ አንብቡት።
ዓይኖቼ ማየት ታክተዋልና በእንቅልፍ እቅፍ ውስጥ ታቅፌ ልተኛበት፤
የክራሩ ብርማ ክሮች ይንዘሩ ነፍስያዬን በእሽሩሩ ያስተኝዋት፤
በገናው ማሲንቆው ሸምነው ዜማ ስልምልም እያለች ያለች ልቤን
በእንዚራቸው ዜማ ዓይነርግብ ያልብሷት የደከማት አቅል ነብሴን

ምትኅታዊ አንደምታው ልቤ ዝንት ዓለም የሚያርፍበት ምቹ አልጋው ነውና
ዱሮዋችንን አዚሙልኝ እያያችሁ ዓይኔ ላይ የቀረውን የማለዳውን ብርሃን ፋና።
የጠዋቷን ፀሐይ ለሰላምታ እጅ እንደሚነሱት አበቦች
እንባችሁን አደራርቃችሁ ቀና በሉ የኔ ውድ ወዳጆች።
በዚህች አልጋዬና በዘላለማዊው የሰማይ ሕይወት መካከል ባለው ክፍተት
እንደ ብርሃን ዓምድ የቆመችውን የሞት ሙሽራ እይዋት ተመልከቷት
ትንፋሻችሁን ዋጥ አርጉና በጸጥታ አዳምጡ ከኔ ጋራ
በነጭ ክንፎቿ እኔን ስትጣራ።
ቀረብ በሉና ሸኙኝ ልሒድበት፤ ፈገግ ባሉ ከንፈሮች ዓይኖቼን ዳብሷቸው።
በድንቡሽቡሽ ጣቶቻቸው ሕፃናቱ እጆቼን ይጨብጧቸው ዘንድ ተዉዋቸው፤
አዛውንቱም የተገታተሩ ደም ሥሮች ባሏቸው እጆቻቸው ግንባሬን ይዘው ይመርቁኝ፤
ድንግል ልጃገረዶች ቀርበው የእግዜርን ጥላ ዓይኖቼ ሥር ይመልከቱልኝ፣
የእሱን ፈቃድ በትንፋሼ ሩጫ የገደል ማሚቶውን ሲያስተገባ ይስሙልኝ።
ክፍል ሁለት - ወደ ላይ መነጠቅ
ከተራራው አናት በላይ አልፌ ሔጂያለሁ፤ ነፍስያዬ በፍጹም ነጻነት የሰማይ ባሕር ሰጥማለች
አጋች የላትም በጣም ርቃ መጥቃ ሔዳለች፤
ርቄ ሔጂያለሁ በጣም፣ እጅጉን ርቄያለሁ ባልንጀሮቼ፣
አመልማሎ ደመናዎቹ ጋርደዋቸዋል ተራሮቹን ከዓይኖቼ።
ሸለቆዎቹ በጸጥታ ባሕር ተውጠዋል አይሰማም ኮሽታ
ጎዳናውና ታዛው በሞላ ተረተዋል በአዚሙ ቱማታ፤
መስኩና የሣሩ ሜዳዎች በሞላ ጋልበው እያለፉ ነው ከአንዳች ነጭ ብርሃን ጀርባ
እንደ ጥር ወር ደመና፣ እንደ ሻማው ነበልባል ለግላጋ ልስልስ ቀዘባ
ድንግዝግዝ ያለ ቀይ ብርሃን ፀሐይ ከቤቷ ስትገባ።
የወጀቡ ዘፈኖችና የዥረቶቹ ቁዘማ እዚህም እዚያ ተበታትነዋል
የሰዎች ሁካታ ረግቦ ተወደዚህ ሙሉ ጸጥታ እዚህ ሰፍኗል፤
አንዳች ነገር አይሰማኝም ከዘላለማዊው ሙዚቃ ሌላ ቅኝት
ፍጹም ሰምሮ ከተስማማው ከዚያ ከነፍስያዬ ጥልቅ ፍላጎት።
ሙሉ ነጭ ካባ ደርቤያለሁ፤
ምቾትና ሰላሜን አግኝቼያለሁ።
ክፍል ሦስት - ቀሪው አካል
ከዚህ ነጭ አቡጀዲ ፍቱኝና ክፈኑኝ እንደገና
የጠንበለልና ሊሊ አባባ ቅጠል በላዪ በትኑና፤
በድኔን አውጡት በዝሆን ጥርስ ከተለበጠው ሳጥን
በአፀደ ብርትኳን በቅጠል ክምር አንተርሱት እራሴን።
ሙሾ አትውረዱ አልሻም የሐዘን እንጉርጉሮ፣ ዘምሩ ስለ ልጅነት ዝፈኑ ስለ ደስታ፤
እንባችሁን አቅቡት፤ መከሩ ደርሷልና የወይኑ ይዘፈን ፍስሐ ይሁን ፌሽታ፤
አንዳችም ሲቃ ድምፅ እንዳይሰማ፤ ይልቁንስ የፍቅርና ደስታን ምልክት
በእጃችሁ ሣሉልኝ ከእኔ ፊት።
በሙሾና በቀንዲል ዜማ ሰላማዊው ድባብ አይደንግጥ አይደንብር፣
ልባችሁ ከልቤ ጋር የዘላለምን ሕይወት ዜማን በስምረት ይዘምር፤
ጥቁር ማቅ ለብሳችሁ አትዘኑ ስለእኔ
ደማቅ ቀለም ለብሳችሁ ተደስቱ እንደኔ፤
ሲቃ ተሞልቶ ልባችሁ አታውሩ ስለኔ፤ ዓይናችሁን ጨፍኑትና
እዩ ተመልከቱ ታገኙኛላችሁ በልባችሁ ሰርክ እንደገና።
በአረንጓዴ ቅጠሎች ጠቅልሉኝና በዝምታ
በሚወደኝ ጫንቃችሁ ተሸከሙኝና በርጋታ
ውስዱኝ ከዚያ ጫካ ማንም ከሌለበት በዝግታ።
በአጥንትና ራስ ቅል ኮሽኮሽታና ጫጫታ እንዳይረበሽ እንዳይሸበር
ይኼን የኔን ግኡዝ ገላ ወስዳችሁ ከዚያ የተጨናነቀ መካነ መቃብር።
ወደ ፅዱ ጫካ ውሰዱኝ ወይን ጠጅና ቀይ አበቦች ከበቀሉበት
ቆፍሩት መቃብሬን ካንዱ ቦታ ያንዱ ጥላ ባንዱ ካላጠላበት።
ደራሽ ጎርፍ መጥቶ አጥንቴን ከኦናው ሸለቆ እንዳይወስደው
መቃብሬ ጥልቅ ሆኖ ይቆፈር ምንም እንዳያውከው፤
ግርማ ሞገሴ ቢገንባት የጠዋቷ ድንግዝግዝ ብርሃን መጥታ
ቁጭ እንድትል ከመቃብሬ በላይ ከላዩ ላይ ወጥታ።
ምንም ምድራዊ ልብስ በድኔን እንዳታለብሱኝ፤
እንደ ፍጥርጥሬ ከእናት መሬት ክርታስ ውስጥ አኑሩኝ፤ በጡቶቿ መሃል ሸጉጡኝ።
በጠምበለል፣ ሊሊ አበባ አፈር ድቤ አልብሱኝ
የእጣን ዛፍ ዘር ለውሳችሁ በላዬ አፍሱብኝ
እና አንድ ቀን ወደፊት ሲያብብ ፍሬ ሲያፈራ ዘሩ
ከልቤ ሙዳይ ይናኝ ዘንድ መልካም መዓዛ ወደ ሰማይ፤
የሰላሜን ምሥጢር ይገልጹላታል ለራሷ ለፀሐይ፤
ከለስላሳ ነፋስ አብረው እየነፈሱ፣ መንገደኛውን ሁላ ያጽናኑት።
ወዳጆቼ በሉ እንግዲህ እዚህ ጋ ተዉኝ - ኮቴያችሁ ሳይሰማ ሒዱ ቦታውን በጸጥታ ተዉት
በሸለቆው መሃል እንደሚጎማለለው ጸጥታ ሒዱ በእርጋታ
ለእግዚአብሔር ተዉኝና እንደ ለውዙና የቱፋሕ ብናኝ ቅጠሎቹ
ሒዱ በለስላሳው አየር በጸጥታ ብን፣ ብን እያላችሁ።
ተመለሳችሁ ዘና ስትሉ በዚያ ዓለም በመኖሪያችሁ
ሞት ከእኔና ከእናንተን ማስወገድ የማይቻለው ምን እንደሆነ ያኔ ታውቁታላችሁ።
እዚህ ያያችሁት ከምድሩ ዓለም እጅግ የራቀ ነውና
ተዉኝና ሒዱ፣ ከዚህ በሰላም ሒዱ።

ካህሊል ጂብራን

መጋቢት 3 ፥ 2011

ትርጉም ብሩክ በየነ
Image may contain: shoes, water and outdoor

Friday, March 1, 2019

ወርሐ ግንቦት


ወርሐ ግንቦት
ግንቦት ፩
·         ፲፱፻፳፰ / - ኢጣልያ ንጉሥ ቪክቶርዮ ኢማኑኤል ሣልሣዊ፣ ኢትዮጵያ ሕዝብ እና ግዛት በኢጣልያ አስተዳደር ሥር የሚያደርግ አዋጅ አስንገረው፣ ይሄንኑ አዋጅ ለዓለም መንግሥታት እንዲሰራጭ አዘዙ። ኢትዮጵያ ንጉሠ ነገሥትነት ማዕርግ ከዚህ ዕለት ጀምሮ የእሳቸውና የወራሾቻቸው እንደሆነ፣ የኢትዮጵያም ሕዝብ እና ግዛት በእንደራሴ እንደሚታደደር በዚሁ አዋጅ ይፋ ተደርገ።
·         ፲፱፻፴፯ / - ኢጣልያ ንጉሥ ቪክቶርዮ ኢማኑኤል ሣልሣዊ፣ ከዙፋናቸው ወርደው ዘውዱ ወደንጉሥ ዳግማዊ ኡምቤርቶ ተዛወረ።
·         ፲፱፻፷፫ / የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሁለተኛው ኢትዮጵያዊ ፓትርያርክ አቡነ ቴዎፍሎስ ስርዓተ ሲመት መንበረ ፀባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ተከናውኗል።
·         ፲፱፻፺፫ / - ጋና ርዕሰ ከተማ አክራ የእግር ኳስ ሜዳ በሚካሄድ ጨዋታ ላይ ተመልካች ሕዝብ በዳኛው ውሳኔ ባለመስማማቱ የተነሳውን ረብሻ ለማብረድ፣ ፖሊሶች የተኮሱት የጢስ ቦምብ ሕዝቡን የባሰውን ሲያተራምሰው በተከሰተው ትርምስና የሰው ግፊያ ፻፳፱ ሰዎች ተቸፍልቀው ህይወታቸውን አጡ።
·         ፲፰፻፵፬ /ራስ መኮንን  ልዕልት ተናኘወርቅ ሣህለ ሥላሴ እና ከደጃዝማች ወልደሚካኤል ወልደ መለኮት ጎላ ወረዳ ደረፎ ማርያም በሚባል ሥፍራ ተወለዱ።
ግንቦት ፪
·         ፲፱፻፹፮ / - ለሃያ ሰባት ዓመታት በእሥራት የቆዩት ኔልሰን ማንዴላ ለአገራቸው ደቡብ አፍሪቃ የመጀመሪያው ጥቁር ፕሬዚደንት በመሆን ቃለ-መሐላቸውን ፈጸሙ።
ግንቦት ፫
·         ፲፱፻፶፪ /ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ “ኢትዮጵያ ንጉሠ ነገሥት መንግሥት የውጭ ጣልቃ ገቦች በአገሪቱ ጉዳይ ውስጥ እየገቡ አስቸግረዋል በሚል መነሻ ፈረንሳይን፤ አሜሪካን፤ ግብጽን፤ የሶቪዬት ሕብረትን፤ ብሪታኒያ እና ዩጎዝላቪያ የልዑካን አለቆች ሰብስበው አነጋገሩ። በማግሥቱ ይፋ የተደረገው ጽሑፋዊ ቃለ-ጉባኤ አምባሳደሮቹ የተጠሩትኢትዮጵያ ንጉሠ ነገሥት መንግሥት በአፍሪቃ ቀንድ አካባቢ ጉዳዮች ላይ የባዕዳንን ጣልቃ ገብነት በብርቱ እንደሚቃወም እና ኢትዮጵያ ግዛትና ሉዐላዊነት ላይ የሚሰነዘሩትን ማናቸውንም እርምጃዎች ለመከላከል ቆራጥ መሆኑን እንዲገነዘቡ ነው።ይላል።
·         ፲፱፻፷፭ /ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ግብጽ ፕሬዚደንት ሳዳት ጋር ለውይይት ወደካይሮ ሲጓዙ፣ እግረ መንገዳቸውን ካርቱም ላይ አርፈው ከፕሬዚደንት ኒሜሪ ጋር ተለወያዩ።
ግንቦት ፬
·         ፲፱፻፶፪ / - ዮርዳኖስ ንጉሥ ሁሴን ለአራት ቀን ጉብኝት አዲስ አበባ ገቡ።
ግንቦት ፭
·         ፲፱፻፷፫ / - በቀድሞው ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ዩኒቨርሲቲ (የአሁኑ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ) ተማሪዎች አድማ መቱ።
·         ፲፱፻፵፱ / - ልዑል መኮንን ኃይለ ሥላሴ መስፍነ ሐረር ናዝሬት መንገድ ሞጆ አካባቢ ላይ በመኪና አደጋ በሞት ተለዩ።
ግንቦት ፮
*********
ግንቦት ፯
*********
ግንቦት ፰
·         ፲፱፻፰፩ ዓ/ም - በኮነሬል መንግሥቱ ኃይለማርያም ላይ የመፈንቀለ መንግሥት ሙከራ ተደረገ።
·         ፲፱፻፴ /ኢትዮጵያዊው የሙዚቃ ምሑር፤ አስተማሪ፤ ደራሲ እና የቅዱስ ያሬድ የሙዚቃ ትምሕርት ቤት መሥራች ዶክቶር አሸናፊ ከበደ በዛሬው ዕለት አዲስ አበባ ተወለዱ።
·         ፲፰፻፷ / - ዓፄ ቴዎድሮስ ሚስት እና ልዑል ዓለማየሁ እናት፤ እቴጌ ጥሩነሽ በዚህ ዕለት አረፉ።
·         ፲፱፻፺ /ኢትዮጵያዊው የሙዚቃ ምሑር፤ አስተማሪ፤ ደራሲ እና የቅዱስ ያሬድ የሙዚቃ ትምሕርት ቤት መሥራች ዶክቶር አሸናፊ ከበደ በዛሬው ዕለት በተወለዱ በስልሳ ዓመታቸው አረፉ።
ግንቦት ፱
·         ፲፱፻፷፫ / - አዲስ አበባ ጄኔራል ዊንጌት ትምህርት ቤት የተመሠረተበትን ፳፭ኛ ዓመት በዓል ንጉሠ ነገሥቱ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ በተገኙበት አከበረ።
ግንቦት ፲
*********
ግንቦት ፲፩
·         ፲፱፻፶፪ / - ኤርትራ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ያጸደቀውን ሕገ-መንግሥቱን በመለወጥ አገሪቱን ኤርትራ መንግሥትወደ ኤርትራ አስተዳደርበመለወጥ ወደፊት ሙሉ ኢትዮጵያ አካል ለማድረግ የሚስችላትን ውሳኔ አጸደቀ።
ግንቦት ፲፪
·         ፲፬፻፹፮ /ዓፄ እስክንድር በነገሡ በ፲፮ ዓመታቸው አረፉና በደብረ ወርቅ ተቀበሩ። ሥልጣነ መንግሥታቸውም ወደ ዓመቱ ልጃቸው ዓምደ ጽዮን ሣልሳዊ ተዘዋወረ። ሆኖም ዓምደ ጽዮን በነገሡ በ፯ ወራቸው ድንገት ስለሞቱ አልጋው ወደ አባታቸው ወንድም አጼ ናዖድ ተላልፏል።
·         ፲፯፻፲፫ /አፄ ዳዊት ሣልሳዊ በዚህ ዕለት አረፉ።
ግንቦት ፲፫
·         ፲፱፻፳፱ / - የካቲት ፲፪ ቀን አዲስ አበባ ላይ ግራዚያኒ ላይ የተወረወረውን ቦምብ ምክንያት በማድረግ ፋሺስቶች ደብረ ሊባኖስ ገዳም ገብተው ፫፻፳ መነኮሳትን በግፍ ጨፈጨፉ፤ ገዳሙንም አቃጠሉ።
·         ፲፱፻፷፮ / - ኢትዮጵያ ንጉሠ ነገሥት መንግሥት አሩሲ ጠቅላይ ግዛት (አሁን አርሲ) እንደራሴ ሆነው የተሾሙትን አቶ ተስፋ ቡሸን የጠቅላይ ግዛቱ ሕዝብ አባሮ አስወጣቸው።
·         ፲፱፻፹፫ / - የኢሕዲሪ (ኢትዮጵያ ሕዝባዊ ዴሞክራሲያዊ ሪፑብሊክ) ፕሬዚዳንትና የኢሠፓ (ኢትዮጵያ ሠራተኞች ፓርቲ) ዋና ጸሐፊ የነበሩት ኮሎኔል መንግሥቱ ኃይለ ማርያም አገር ጥለው በመኮብለል ዚምባብዌ ገቡ።
·         ፲፱፻፳፱ / - ኮሎኔል መንግሥቱ ኃይለ ማርያም በዚህ ዕለት አዲስ አበባ ተወለዱ።
ግንቦት ፲፬
*********
ግንቦት ፲፭
*********
ግንቦት ፲፮
·         ፲፱፻፹፫ /ኤርትራ ኢትዮጵያ ተገንጥላ ራሷን የቻለች ሉዐላዊ አገር ሆነች።
ግንቦት ፲፯
·         የአፍሪቃ አንድነት ድርጅት የተመሠረተበትን ዕለት በማስታወስ ይህ ዕለት በመላው አፍሪቃ አኅጉር የአፍሪቃ ቀን ተብሎ ይከበራል።
·         ፲፱፻፶፭ / - የ፴፪ ነጻ አፍሪቃ አገራት መሪዎች አዲስ አበባ ላይ ተሰብስበው የአፍሪቃ አንድነት ድርጅት መሠረቱ።
·         ፲፱፻፷፫ / - አዲስ አበባ የሁለተኛ ደረጃ ተማሪዎች ሰላማዊ ሰልፍ፤ በከተማው አውቶብሶች እና ንብረት ላይ ጉዳት አደረሱ። በዚህም ምክንያት አሥር ሁለተኛ ደረጃ ትምሕርት ቤቶች ተዘጉ።
ግንቦት ፲፰
·         ፲፯፻፲፫ / - ከወህኒ በወረዱ በሁለተኛው ቀን አፄ አድያም ሰገድ ኢያሱ ልጅ አፄ በካፋ ጎንደር ላይ በጳጳሱ አባ ክርስቶዶሉ እና እጨጌ ተክለ ሃይማኖት ተቀብተው ነገሡ።
·         ፲፱፻፶፪ / - ሶቪዬት ሕብረት የኢንዱስትሪ እና የቴክኒክ ምርቶች አውደ ርዕይ አዲስ አበባ ላይ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ተመርቆ ተከፈተ።
·         ፲፱፻፷፭ /የአፍሪቃ አንድነት ድርጅት አሥረኛው የመሪዎች ስብሰባ አዲስ አበባ ተከፈተ።
ግንቦት ፲፱
·         ፲፱፻፷፮ / - ኤርትራ ነጻ አውጪ ግንባር አባላት ጊንዳ ውስጥ በሉተራን ሚሲዮን ሆስፒታል ውስጥ የሚሠራ ዶክቶርን የመጥለፍ ሙከራ ሲያደርጉ አንዲት አስታማሚ (ነርስ) ተገደለች።
·         ፲፱፻፷፮ / - የቴሌኮሙኒኬሽን ሠራተኞች በአድማ ሥራቸውን አቆሙ።
ግንቦት ፳
·         ፲፱፻፷፮ / - የጠቅላይ ሚኒስትር እንዳልካቸው መኮንን መንግሥት የሚኒስትሮችን ለውጥ ይፋ አደረገ። ከነዚህም አንዱ የአገር ግዛት ሚኒስትር የነበሩትን ደጃዝማች ዘውዴ ገብረ ሥላሴ ወደ ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር መዛወር ያካትታል።
·         ፲፱፻፹፫ /ኢሕአዴግ በዘመቻ ወጋገን አዲስ አበባ ተቆጣጠረ። አቶ መለስ ዜናዊ የሽግግሩ መንግሥት ፕሬዚዳንት ሆኑ።
ግንቦት ፳፩
·         ፲፰፻፸ / አፄ ዮሐንስ እና ሸዋ ንጉሥ ምኒልክ በተገኙበት ወሎ ቦሩ ሜዳ ላይ የተካሄደው የሃይማኖት ክርክር እልባት አገኘ፡፡
ግንቦት ፳፪
·         ፲፱፻፷፮ / - ኢትዮጵያ ሕዝባዊ አመጽ ቆስቋሽነት የተሠየመው የሙስና እና የሥልጣን በደል መርማሪ ሸንጎ ሥራውን የሚመራበት ሕግ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ጸደቀ።
ግንቦት ፳፫
·         ፲፱፻፯ /ልጅ ኢያሱ አባታቸውን ራስ ሚካኤል ደሴ ላይ ንጉሠ ወሎ  ትግሬ ብለው አነገሧቸው።
ግንቦት ፳፬
·         ፲፱፻፶፫ / - በ፳ኛው መቶ ክፍለ ዘመን በትልቅነቱ ኢትዮጵያ ታሪክ አቻ የሌለው ሪክተርሚዛን ስድስት ነጥብ ሰባት ያስመዘገበ የመሬት እንቅጥቅጥ ተከስቶ የማጀቴን ከተማ ሲደመስስ፣ በጎረቤቷ ካራቆሬ ደግሞ ከመቶ እጅ አርባ አምሥቱ መኖሪያ ቤቶች ወድመዋል። ከካራቆሬ በስተሰሜን የሚያልፈው ዋናው አዲስ አበባ አስመራ መንገድ እና ድልድዮችም እንቅጥቅጡ ባስከተለው የድንጋይ ናዳ ወደ አሥራ ሰባት ኪሎ ሜትር ርዝመት ላይ አደጋ ደረሰ
ግንቦት ፳፭
·         ፲፯፻፹፰ / - አመድ ከሰማይ ዘነበ።
·         ፲፱፻፳፩ / - ግብጽ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ የመጀመሪያዎቹን አራት ኢትዮጵያውያን ጳጳሳት (አቡነ አብርሓም - ጎንደር እና ጎጃም አቡነ ይስሐቅ - ትግሬ እና የስሜን፤ አቡነ ጴጥሮስ ወሎ እና የላስታ፤ አቡነ ሚካኤል - ኢሉባቡር እና የምዕራብ ኢትዮጵያ) ከግብጻዊው ሊቀ ጳጳሳት (አቡነ ቄርሎስ)ጋር ካይሮ ላይ ተቀብተው ተሾሙ።
ግንቦት ፳፮
·         ፲፯፻፷፭ / - ዓፄ በካፋ ሚስት የነበሩት እቴጌ ምንትዋብ በዚህ ዕለት አርፈው በቁስቋም ደብረ ጸሐይ ማርያም ቤተ ክርስቲያን ተቀበሩ።
ግንቦት ፳፯
·         ፲፱፻፷፭ / - በመከላከያ ሚኒስትር ጄኔራል ሊዩቢቺክ የሚመራ ዩጎዝላቪያ ወታደራዊ ቡድን ኢትዮጵያ ንጉሠ ነገሥት መንግሥት ጋር አዲስ አበባ ላይ ያካሄደውን የአራት ቀን ውይይት ጀመረ።
ግንቦት ፳፰
·         ፲፱፻፹፫ / - በአዲስ አበባ ከተማ በቆሎ ሰፈር አካባቢ የሚገኝ ወታደራዊ ካምፕ ውስጥ በተነሣ ፍንዳታ በርካታ ሕይወት አለፈ፤ ብዙ ቤቶችና ንብረት ላይ ጉዳት ደረሰ።
ግንቦት ፳፱
*********
ግንቦት ፴
·         ፲፱፻፴፫ /አዲስ ዘመን በሚለው መጠሪያ የሚታወቀው ብሔራዊ ጋዜጣ በይፋ ሥራ ጀመረ። የጋዜጣው ሥያሜ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ከጠላት ወረራ በኋላ ሚያዝያ ፳፯ ቀን ፲፱፻፴፫ / በድል አድራጊነት ሲገቡ «ይህ የአዲሲቷ ኢትዮጵያ የአዲስ ዘመን መጀመሪያ ነው» ማለታቸውን መሠረት ያደርጋል።
·         ፭፻፴ / - ኢትዮጵያ ንጉሠ ነገሥት ዓፄ ካሌብ አረፉ።