Thursday, December 27, 2018

አዲስ አባ

አዲስ አባ
 
ለፈላጊዋ ሰፍታ ለተፈላጊዋ ጠባ
አዲስ ከተማ ጫካ ሸገር ወጣ ገባ
ሲመሽ እየነጋች በቀን ሌት ደምቃ
ሀብታም ከነዳይ አንድ ላይ አምቃ
አዱ ገነት የአምባዎች ሁሉ አናት
ሰማይ ጠቀስ ያገር እርግብግቢት
ባራት አፍ ውጣ ባራት አፍ ተፍታ
ያገር እስትንፋስ ያገር ልብ ትርታ
ሚሊዮን ፀንሳ ሚሊዮን ወልዳ
ሚሊዮን አስይዛ ሚሊዮን ሰዳ
በሰፈር መንደሯ ራሷን አዳቅላ
ሽቅብ ቁልቁል ወርዳ ተሰቅላ
የአብራኳን ከጉዲፈቻ እኩል ዐይታ
ከሊቅ እስከ ደቂቅ ሁሉንም አንሥታ
እኩይ ከጻዲቅ ጡቷን የምታጠባ
የሰው ዘር እናት አዲስ፣ አዲስ አባ
ለፈላጊው ሰፍታ ለተፈለገው ጠባ
አዲስ የሰው ጫካ ሸገር ወጣ ገባ
ትሳስ ኪዳነምህርት ለዐሥራ ሰባት አጥቢያ ተሌቱ 8 ሰዓት ተአምስት ከእንቅልፍ መሃል መጥቶ የተቸከቸከ (2018)
ብሩክ በየነ

Tuesday, December 11, 2018

ካልሲና ጫማ


ካልሲና ጫማ
ዕድሜው በግምት ወደ ዐሥር ዓመት የሚጠጋ ሕፃን፣ ባዶ እግሩን ከአንድ የጫማ መደብር መግቢያ በር ጎን ባለው መስታውት ውስጥ የተሰቀሉትን ጫማዎችና ካልሲዎች አንድ ባንድ አማርጦ እያየ ነበር። ጊዜው ክረምት ስለነበር ብርዱ ቆፈን ያስይዛል። እያንዘፈዘፈውም ቢሆን ብላቴናው ከሱቁ በር ላይ ቆሞ በተመስጦ ጫማዎቹን አንድ ባንድ ያያል።
በዚህ መሀል ታዲያ በሱቁ አጠገብ ታልፍ የነበረች አንዲት ደርባባ ሴትዮ ድንገት ልጁን ዐየችውና በሁኔታው ልቧ ተነካ።
“ማሙሽዬ፣ ምንድነው በመስታውቱ ውስጥ እያየህ ያለኸው?” ስትልም ጠየቀችው።
“እግዚአብሔርን ጫማ እንዲሰጠኝ እየጠየቅኩት ነው!”
የሰጣት መልስ ውስጧ ድረስ ገብቶ እንደ ኤሌክትሪክ ሲነዝራት ተሰማት። ልጁን በእጇ ወዲያውኑ አፈፍ አድርጋ ይዛው ሳታመነታ ወደ ሱቁ ውስጥ ገባች። ባለሱቁንም ግማሽ ደርዘን ካልሲ እንዲያመጣላት አዘዘችው። ባለሱቁም የረዥም ጊዜ ደንበኛውን ለማስደስት ወዲያው እንደተባለው አደረገ። ቀጠለችና ደግሞ ውኃ በማስታጠቢያና ፎጣ እንዲያዘጋጅላት ጠየቀችው። ባለሱቁም ይህንንም ግራ እየተጋባ ታዘዛት። ሕፃኑን ከመደብሩ ጓሮ ባለው ቦታ ይዛው ገባችና ከንዱ ጥግ አስቀመጠችው። እግሮቹን ማስታጠቢያው ውስጥ እንዲነክራቸው ካደረገችው በኋላ እጅጌዋን ሰብስባ በመንበርከክ እግሮቹን አጠበችውና በፎጣው አደራረቀቻቸው።
ምልክት ስትሰጠው ባለሱቁ ቅድም የጠየቀችውን ካልሲዎቹን ይዞላት መጣ። ከካልሲዎቹ መካከል ደስ ያለውን እንዲመርጥ ለልጁ ሰጠችው። አዲስ ካልሲም እሷ እያገዘችው እግሩ ላይ አጠለቀ። አዲስ ጫማም ቀጥላ አስደረገችው። አንድ ሁለቴ ወደፊትና ወደኋላ እንዲራመድ ካደረገችው በኋላ፦
__ “ማሙሽዬ፣ አሁን መቼስ፣ ያለጥርጥር ደስ ብሎሃል?” አለችው እንዲያው ለወጉ ያህል። ደስ እንዳለው ምን ያጠራጥራል ?
ልጁ በርግጥ ምንም መናገር ሆነ ምንም ዓይነት መልስ መስጠት አልቻለም። እየሆነ ባለውና እያየው ባለው ነገር ሁሉ እውነትነት እጅግ ተጠራጥሯል። በደስታ ብዛት አንደበቱ ክዶታል። ደንዝዞ እንደ ሐውልት ቆሟል።
ሴትየዋ የሚከፈለውን ከፍላ ልጁን እዛው ሱቁ ውስጥ እንደተገተረ ትታው ልትሔድ ስትል ከኋላዋ ሮጦ ደረሰባት። እጇን ነካ፣ ነካ አድርጎ ጠራትና ዞር ስትል፤ እንባ ባረገዙ ዓይኖች ዓይን ዓይኗን እያያት፣ ሳግ እየተናነቀው፦
“እትዬ ! የእግዚአብሔር ሚስት አንቺ ነሽ እንዴ ?” ብሎ ጠየቃት።

Saturday, December 1, 2018

የስድስት ዓመቱ ብላቴና አስደማሚ ታሪክ


የስድስት ዓመቱ ብላቴና አስደማሚ ታሪክ
ብስለት እንዲህ ዝምብሎ የሚገኝ የዋዛ ነገር አይደለም። ሁሉም ሰው በየራሱ መንገድ፣ ያጣጥመዋል። ብስለት ደረጃ ላይ የምንደርስበት ዕድሜ እንደ መልካችን ሁሉ ካንዳችን ላንዳችን የተለያየም ነው። አንዳንድ ሰዎች ገና ጨቅላ እያሉ የብስለት ደረጃ ላይ ሲደርሱ ሌሎች በምድር ላይ ዘመናትን ቢያስቆጥሩም ይህ ነው የሚባል የአእምሮ ብስለት ደረጃ ላይ ሳይደርሱ ያልፋሉ። እንግዲያው የዛሬው ወጋችን የሚያጠነጥነው ካንተና ከኔ ቀድሞ ገና በስድስት ዓመቱ የብስለት ደረጃ ላይ ስለ ደረሰ ብላቴና ይሆናል። ለምን እንዲህ እንዳልኩ እስከ መጨረሻው አንብብና በፍረጃዬ ትስማማለህ ብዬም ተስፋ አደርጋለሁ።
ብስለት

ወጋችንን ከመጀመራችን በፊት ስለ ብስለት ትንሽ ነገር ለመናገር ያክል “ብስለት” አንድን ሰው እንዲህ ነው ብለህ ልታሳየውና ልታስተምረው ወይም አንተም ራስህ ከሌላ ሰው ልትማረው የምትችለው ነገር አይደለም። ከጊዜ ጋር የምትደርስበት የአእምሮ ጥንካሬ ደረጃ ነው። ለአንዳንድ ሰዎች፣ ገና በአፍላ ዕድሜያቸው ሲጎበኛቸው፣ ለአንዳንዶች ግን ከመምጣቱ በፊት ሊዘገይባቸው ይችል ይሆናል!

ይህን የስድስት ዓመት ብላቴና እንደ አብነት እንውሰደው። ይህን ታሪክ አንብብና ስለምን እያወራን እንዳለን ይበራልሃል!
ታሪኩ
እንግዲህ ታሪክ በአጭሩ ይህን ይመስላል...

የስድስት ዓመት ልጅ ከታናሽ እህቱ ጋር የቀለጠ የገበያ ማዕከል ውስጥ ብቻቸውን ወዲህና ወዲያ በእግራቸው እየተንሸራሸሩ ነበሩ። ብዙ ከተንሸራሸሩ በኋላም ትንሿ እህቱ አንድ ሱቅ መስኮት ላይ ቆም አለች። እህቱ ወደ ኋላ መቅረቷን ያስተዋለው ታላቅየው ወንድሟ ወደ ኋላው መለስ ይልና ምን ወደ ኋላ እንዳስቀራት ተመለከተ። ቀልቧን የሰረቀው ነገር ምን እንደሆነም ወዲያው ገባው። እህቱ እንዲያ በተመስጦ የምታየው ያለችው በሱቁ ውስጥ ያለውን የሚሸጥ አሻንጉሊት እንደሆነ ለመረዳት ቅጽበት እንኳ ጊዜ አልወሰደበትም።
ብላቴናው እህቱ አሻንጉሊቱን በርግጠኝነት መፈለጓን መረዳቱን በሚያሳይ መልኩምን የሆነ የምትፈልጊው ነገር አለ አንዴ?” ሲል ጠየቃት። እህትየውም ምን እንደምትፈልግ ዓይኗን ከሱቁ መስኮት ላይ ሳታነሳ በእጇ አሻንጉሊቷን በመጠቆም አሳየችው።  ብላቴናውም አሻንጉሊቷን ዐየት አደርጎ እንደ ቁምነገረኛ ታላቅ ወንድም እህቱን በእጇ ይዞ ወደ ሱቁ ይዟት ገባ። ከመደርደሪያው ላይ ፍጹም በሆነ በራስ መተማመን መንፈስ አንሥቶ ለእህቱ አሻንጉሊቷን ሰጣት። እህትየው ወንድሟን ቀና ብላ ዐየችውና ፈገግ አለች። በጣም መደሰቷን ከፊቷ ላይ ማንበብ ይቻላል።
ባለሱቁ

ባለሱቁ ይህ ሁሉ ሲሆን ከመጀመሪያው ጀምሮ በጥንቃቄ እያንዳንዷን ነገር እየተመለከተ ነበር። በዚህ ልጅ ሁኔታ በጣም ተገርሟል። እህቱ በመደሰቷ የረካው ትንሹ ልጅ ወደ ሱቁ ሒሳብ መክፈያ ሣጥን መጣን ባለሱቁን ኮራ ብሎ “ ጋሼ፣ የዚህ አሻንጉሊት ዋጋ ስንት ነው? !” ሲል ጠየቀ። 

ይህ ባለሱቅ እንደ ዕድል ሆኖ ፍጹም ደግ ሰው መሆኑን ከግምትህ አስገባና ምን ሊያደርግ እንደሚችል ገምት። የነዚህን ወንድምና እህት ፍቅር በማየት ልቡ በርህራሄ ቀለጠ። ረጋ ባለ ድምፀት ቀስ ብሎ ለትንሹ ገራሚ ልጅስንት መክፈል ትፈልጋለህ?” ሲል ጠየቀው።
የቀንድ አውጣ ቅርፊቶች
ልጁ ምንም ገንዘብ እንዳልያዘ ያው የታወቀ ነው። ግን ከባሕሩ ዳርቻ የለቃቀማቸውን የቀንድ አውጣ ቅርፊቶች በኪሱ ይዞ ነበር። እህቱ ለወሰደችው አሻንጉሊት ሒሳቡን ለመክፈል ሁሉንም የቀንድ አውጣ ቅርፊት ከኪሱ አወጣና ለባለ ሱቁ ተንጠራርቶ ጠረጴዛው ላይ ዘረገፈለት። 

ባለሱቁም የእውነት ገንዘብ የተከፈለው ይመስል ቅርፊቶቹን አንድ ባንድ እያነሳ ቆጠራቸው። ቆጥሮ ሲጨርስም ሕፃኑን ልጅ ቀና ብሎ ዐየው፣ ልጁም እንደ መጨነቅ አለና ምነው አይበቃም?” ሲል በፍራቻ ጠየቀው። የልጁን ጭንቀት ያስተዋለው ባለሱቅ ኧረ እንዲያውምየሰጠኸኝ ከዋጋው በላይ ነው። ስለዚህ ትርፉን እንካ መልሼልሃለሁ፣ ያንተ ነው ያዘውአለው። እንዲህ ብሎ ሁሉንም መልሶለት ለራሱ ያስቀረው ዐራት የቀንድ አውጣ ቅርፊት ብቻ ነበር። ብላቴናው በጣም ተደሰተና ከትንሿ እህቱ ጋር አመስግኖ ከሱቁ ወጥቶ ሔደ።
እውነተኛው ጥያቄ
ከባለሱቁ ጋር የሚሠራ ሌላ ተቀጣሪ ሠራተኛ ባለሱቁ እየሠራ ያለውን ሥራ እየተከታተለ ነበርና በነገሩ በጣም ተገረመ። ወደ ባለሱቁ ጠጋ አለና አለቃ! ያን የመሰለ ውድ አሻንጉሊት እንዴት በዐራት የቀንድ አውጣ ቅርፊት ትለውጣለህ ???” ሲል ጠየቀው። ባለሱቁ ፈገግ ብሎ ለሠራተኛው እንዴት መሰለህ፣ እነዚህ ለኛ የማይረቡ የቀንድ አውጣ ቅርፊቶች ናቸው። ግን ለዚያ ትንሽዬ ልጅ ከምንም በላይ ውድ ነገር ናቸው። እና በዚህ ዕድሜው፣ ገንዘብ ምን ማለት እንደሆነ አይገባውም። ሆኖም ሲያድግ የገንዘብ ትርጉም ምን እንደሆነ ያኔ ያውቃል። በገንዘብ ሳይሆን በቀንድ አውጣ ቅርፊት አሻንጉሊት እንደገዛ ትዝ ሲለው ቀን እኔን ያስበኛል። በዚህም ዓለም ሁሉ በቀና ሰዎች የተሞላች ስለመሆኗ ያስባል። በዚህም ቀና አመለካከት በውስጡ እንዲያጎለብትና ጥሩ ሰው ለመሆን እንዲችል ይበረታታል።

ሁላችንም ከዚህ አንድ ወይም ሁለት ጥሩ ነገር መማር አለብን። ሁላችንም ቀና መንፈስን ብናሠራጭ እና መልካም ባሕሪ ለማሳየት ብንታትር፣ ዓለማችን ምንኛ ደግ በሆነች ነበር ?!
ሱሃስ ከተባለ/ች ጸሐፊ በበይነመረብ ላይ ተገኝቶ በከሣቴ ብርሃን ቡሩክ ወደ አማርኛ ስለ ቀናነት ዋጋ ለመክፈል ጊዜ ተሰውቶ የተተረጎመ ኅዳር 22፥ 2018 (በራስ አቆጣጠር)